የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ በአዋጅ ቁጥር 532/1999 ዓ.ም የፀደቀውን የምርጫ ሕግ መሰረት በማድረግ በደንብና መመሪያዎቹ ላይ የተደረገውን የማሻሻያ ሐሳብ አስመልክቶ ለፓርቲው በላከው ሰነድ ላይ ያለውን አቋም ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በደብዳቤ አሳወቀ፡፡
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ በመጋቢት ወር 2ዐዐ1 ዓ.ም ለሁሉም ፓርቲዎች በላከው ሰነድ በአዋጁ መሰረት አራት ደንቦችና ስድስት መመሪያዎች ያሉት የማሻሻያ ሐሳብ ሲሆን እያንዳንዱ ፓርቲ በመመሪያውና በደንቡ ላይ ያለውን ቅሬታ እንዲገልጽና መሻሻል የሚገባቸውን ነጥቦች በጽሑፍ ለቦርዱ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንዲያስገባ የሚያሳስብ ነው፡፡
መኢአድ ከምርጫ ቦርድ የተላከውን ሰነድ የሚያጠና ኮሚቴ አቋቁሞ በአዋጁ፣ በደንቦቹንና በመመሪያዎቹ ላይ ሰፊ ጥናት አድርጓል፡፡ በመሆኑም ከመመሪያውና ከደንቡ ይልቅ መሰረታዊ ማሻሻያ መደረግ ያለበት በአዋጁ ላይ መሆኑን አጥብቆ እየገለፀ ይገኛል፡፡
መኢአድ በጻፈዉ ደብዳቤ ላይ ገዢው ፓርቲ ለራሱ እንደሚመቸው አድርጐ ያስቀመጣቸውን አንቀጾች አገርና ሕዝብን በሚጠቅም መልኩ መሻሻል እንዳለባቸውና አሁን ባለው ሁኔታ ግን ሕጉ አሳሪ ሆኖ እያለ ተሻሽሏል ማለት እንደማይቻል ጠቅሷል፡፡ ይህም በመሆኑ መኢአድ ከምርጫ ቦርድ መመሪያና ደንብ መሻሻል በፊት መንግስት በ1999 ዓ.ም በፓርላማ ያፀደቀውን አዋጅ 532/1999 /ተሻሽሎ የወጣው የምርጫ ሕግ/ በድጋሚ መሻሻል አለበት ብሏል፡፡
መኢአድ ከ41 አንቀጾች በላይ መስተካከል አለባቸው በማለት አንቀጾችን በዝርዝር ያስቀመጠ ሲሆን አንቀጾቹ ሊስተካከሉ የሚችሉበትን አማራጭ ሐሳብ የያዘ ሰነድ አቅርቧል፡፡
የምርጫ አዋጅ ቁጥር 532/1999 ማሻሻያ እንደተደረገበት በምርጫ ቦርድ ቢገለጽም በአዋጁ ውስጥ ያሉ ብዙ አንቀጾች መሻሻል እንዳለባቸው መኢአድ ያስገነዝባል፡፡ ዋናው አዋጅ ገንቢ በሆነ መንገድ እስካልተሻሻለ ድረስ ደንቦቹና መመሪያዎቹ የተፈለገውን ውጤት ሊያመጡ እንደማይችሉ ይገልጻል፡፡ ለዚህም ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ በመወያየት አዋጁ እንዲዳብር ማድረግ አስፈላጊ ነው ሲል መኢአድ ሐሳቡን አቅርቧል፡፡ የአዋጁ መሻሻል በ2ዐዐ2 ዓ.ም ለሚካሄደው አገራዊ ምርጫ ነጻ፣ ፍትሃዊና ሰላማዊ መሆን ወሳኝ ነው በማለት ገልጿል፡፡
መኢአድ ይህን አቋሙን የሚገልጽ ሁለት ገጽ ደብዳቤና ስምንት ገጽ የማሻሻያ ሐሳብ ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የጻፈ ሲሆን ለምርጫ ቦርድና ለሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎችም መላኩ ታውቋል፡፡