በምስራቅ ጐጃም ዞን በአዋባል ወረዳ ሉማሜ ከተማ መጋቢት 4 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም አንድ ተማሪ በታጣቂዎች መገደሉን ምንጮች ለአንድነት ጋዜጣ ገለፁ፡፡
የቅድመ መሰናዶ የ 12ኛ ክፍል ተማሪ የነበረው ተማሪ ተገኑ ጌታቸው መጋቢት 4 ቀን ምሽት ላይ ከመኖሪያ ቤቱ ሲወጣ በታጣቂዎች ጥይት ተመቶ መሞቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ሟችና ቤተሰቦቹ የመኢአድ አባልና ደጋፊዎች እንደነበሩ ምንጮቻችን ገልፀው በወቅቱ በመንደሩ ውስጥ በሌሎች ሰዎች መካከል ግጭት ተፈጥሮ ስለነበር ለማየት ከቤቱ ሲወጣ በተገኘው አጋጣሚ በታጣቂዎች ጥይት ሊመታ መቻሉን አስረድተዋል፡፡
በእለቱ ምሽት ላይ ተማሪው በተከራየው መኖሪያ አካባቢ የተፈጠረውን አለመግባባት ምክንያት በማድረግ አራት ታጣቂዎች ወደ መኖሪያ ቤቱ በመዝለቅ ሆን ብለው ሟቹን በተደጋጋሚ በጥይት እንደመቱት የአይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ በተጨማሪም ከመኖሪያ ቤቱ ውጭ ሌሎች ቁጥራቸው ያልታወቁ ፖሊሶች እንደነበሩና ሟቹን በጥይት ከመቱ በኋላ መሰወራቸውን ተናግረዋል፡፡
በጥይት የተደበደበው ተማሪ ምንም አይነት የሕክምና እርዳታ እንዳልተደረገለትና ከምሽቱ አምስት ሰዓት አካባቢ ሲሆን ታጣቂዎችና ፖሊሶች የሟችን አስከሬን በመኪና በመጫን ወላጆቹ ወደሚኖሩበት አካባቢ በመውሰድ ሜዳ ላይ ጥለውት እንደተሰወሩ የአይን ምስክሮች አስረድተዋል፡፡
ወንጀሉን ከፈፀሙ ታጣቂዎች ውስጥ አንዱ እጁን ለፖሊስ መስጠቱንና ሶስቱ መሰወራቸውን የደረሰን መረጃ ይጠቁማል፡፡
የተገኑ ጌታቸውን በግፍ መገደል ተከትሎ የሚማርበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ከፍተኛ ተቃውሞ ያሰሙ ሲሆን ለአምስት ተከታታይ ቀናት ያሕልም ት/ቤቱ ተዘግቶ እንደቆየ አብራርተዋል፡፡