በሰሜን ጐንደር ዞን በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎችና ማረሚያ ቤቶች የሚገኙ እስረኞች ድብደባ እንደሚፈፀምባቸውና እንደሚጉላሉ ከስፍራው የደረሰን መረጃ ይጠቁማል፡፡
በፖሊስ ጣቢያዎቹ የሚገኙ ወንጀል መርማሪዎች የበዛ ኃይል እንደሚጠቀሙና አንዳንድ ጣቢያዎችም የተዘጋጁ የማሰቃያና የመደብደቢያ ክፍል እንዳላቸው ታውቋል፡፡
የሕግ ታራሚዎቹ እንደሚሉት ፖሊስ ጣቢያዎቹ በሕግ ሳይሆን በግለሰቦች ትእዛዝ ይሰራሉ፤ በራሳቸው ስልጣን ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ያስራሉ፤ የዋስትና መብት ይከለክላሉ፤ በዋስ ፍ/ቤቱ የለቀቃቸውን ሰዎች አይፈቱም፤ በዋስ ወይም በነጻ የተለቀቁ ግለሰቦችን ያለ ፍ/ቤት ትእዛዝ መልሰው ያስራሉ ብለዋል፡፡
ፖሊስ ጣቢያዎቹ የፍ/ቤቱን ትእዛዝ እንደማይፈጽሙና አንዳንድ የፖሊስ አባላትና ኃላፊዎችም ሹመት ለማግኘት ሲሉ ግለሰቦችን በሐሰት እንደሚከሱ ገልፀዋል፡፡