የጐፋ ልዩ ዞን የገዢው ፓርቲ የጽ/ቤቶቹን ባንዲራ እያወረደበት መሆኑን መኢአድ ገለፀ
በጐፋ ልዩ ዞን መኢአድ ጽ/ቤትና ባስኬቶ ልዩ ወረዳ መኢአድ ጽ/ቤት በተለያዩ ጊዜያት የመንግስት ፖሊሶችና ባለስልጣናት ታፔላዎችንና ሰንደቅ ዓላማዎችን በማውረድ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት እየፈፀሙብን ነው ሲሉ የመኢአድ የጐፋ ልዩ ዞን ኮሚቴ ሰብሳቢና የፓርቲው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት አቶ እንድርያስ ኢሮ ለአንድነት ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ገልፀዋል፡፡
አቶ እንድርያስ ኤሮ “በፓርቲው ላይ እየተፈጠረ ያለውን ችግር ለመጠቆም ብንሞክርም የጐፋ ልዩ ዞን የሚለውን አወቃቀርና ታፔላ አንቀበልም ያሉን ሲሆን በምርጫ ቦርድ አዋጅ ቁጥር 46/85 መሰረት ማንኛውንም እውቅና ያለው ፓርቲ የራሱን ጽ/ቤት የመክፈት መብት አለው ብንላቸውም መንግስት ሳያፀድቅ ይህንን ማድረግ አትችሉም የሚል መልስ ነበር የሰጡን፡፡ እኛ ግን የፓርቲያችን ላእላይ ምክር ቤት ወስኖ ፕሬዝዳንታችን ካፀደቁት መክፈት እንችላለን በማለት ብንሟገታቸውም በስተመጨረሻ ይህ ጉዳይ የሚመለከተው ፍርድ ቤቱን ነው በማለት እንዳንሰራ አውከውናል፡፡” ብለዋል፡፡
የገዢው ፓርቲ ታዛዦች ከፍርድ ቤት ትእዛዝ ውጭ በአቃቤ ሕግ ብሩክ አባተ በመመራት የዞኑን የመኢአድ ሶስት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት አስረው እንደነበርም ተገልጿል፡፡ አቶ እንድርያስ ኢሮን የካቲት 5 ቀን ረፋዱ ላይ በመያዝ ለአንድ ቀን ያህል አስረው በዋስ ሲፈቷቸው፣ የዞኑ ፀሐፊ አቶ አበበ ኢልዳድን እና አቶ ሐብታሙ ዱባኤን ከየካቲት 5 ቀን እስከ የካቲት 12 ቀን ድረስ ያለፍርድ ቤት ትእዛዝ ካሰሯቸው በኋላ በሰባተኛው ቀነ ጉዳዩን ለከፍተኛው ፍርድ ቤት በማቅረብ በዋስ ተለቀዋል ያሉት አቶ እንድርያስ ሌሎቹንም አባሎቻችንን በዚህ መሰሉ ሕገ ወይ ተግባር እያንገላቷቸው ነው ብለዋል፡፡
የካቲት 24 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ከቀኑ 11፡1ዐ ላይ የመኢአድ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን በማሰር የሚታወቁት አቃቤ ሕጉ አቶ ብሩክ አባተ ወደ መኢአድ ጽ/ቤት በመምጣት ታፔላውን በመንቀልና ሰንደቅ ዓአላማውን በማውረድ በመኪና ጭነው መሄዳቸው ታውቋል፡፡ በማግስቱም የመኢአድ የዞኑ የ12 ወረዳ ሰብሳቢዎች በአንድ ላይ ሆነው ጐፋ አካባቢ ፍትሕ ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በመሄድ ንብረታች መሰረቁን ጠቅሰው፣ የጽ/ቤቱን ዘበኛ በማስፈራራት ንብረቱን የዘረፋት ግለሰብ ለፍርድ ሊቀርቡልን ይገባል ብለው ቢከሱም ሶስት ጊዜ በቀጠሮ ካመላለሷቸው በኋላ በመጋቢት 8 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም የፍትሕ ማስተባበሪያ ጽ/ቤቱ እናንተ ክስ ላይ ስላላችሁ እንደገና ሌላ ክስ /ፋይል/ አንከፍትም የሚል መልስ እንደሰጧቸው ከስፍራው ከደረሰን መረጃ ለማወቅ ተችሏል፡፡