የመኢአድ የደጀን ወረዳ ልዩ ዞን የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት አካሄድ
በምስራቅ ጐጃም ዞን የደጀን ልዩ ወረዳ የመኢአድ አባላት ለሴቶችና ወጣቶች ምክር ቤት ማጠናከሪያ የሚሆን የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ያካሄደ መሆኑ ተገለፀ፡፡
የካቲት 28 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በደጀን ከተማ ከቀኑ 4 ሰአት እስከ 7 ሰዓት ተኩል ድረስ በቆየዉ ልዩ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት ላይ በርካታ የአመራር ሐላፊዎችና አባላት ተሳታፊ እንደነበሩ ታውቋል፡፡ ከመኢአድ ዋና ጽ/ቤት ተወክለው የክብር እንግዳ የሆኑት የመኢአድ ምክትል ፕሬዝዳንትና የምዕራብ ቀጠና ኃላፊ አቶ አሰፋ ኃብተወልድ እና የሰሜን ቀጠና አደራጅ መቶ አለቃ ወንድም ደፋር በዝግጅቱ ላይ ተገኝተው ስለ አደረጃጀትና ስለወቅቱ ተጨባጭ ሁኔታ እንዲሁም መኢአድ እያከናወነ ስላለው የማደራጀት ሂደት በሠፊው ገልጸዋል ፡፡
በገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅቱ ላይ ቲሸርትና መጽሐፍ የሚያስገኙ እጣዎች ተዘጋጅተው የቀረቡ ሲሆን የምግብና የመጠጥ ሽያጭም የገቢ ማሰባሰቢያው አንድ አካል የነበረ መሆኑ ታውቋል፡፡
በዝግጅቱ ላይ ከሶስት መቶ በላይ ተሳታፊ አባላትና ደጋፊዎች እንደተገኙና ሥነ ሥርአቱም እጅግ ያማረ እንደነበር ወደፊትም ሊበረታታ እንደሚገባውና ለሌሎችም ወረዳዎች አርአያ እንደሚሆን ከመኢአድ ዋና ጽ/ቤት ተጋብዘው የተገኙት አቶ አሰፋ ኃብተወልድ ገልፀዋል፡፡
ለሴቶችና ለወጣቶች ምክር ቤት ማደራጃ እንዲሆን ታስቦ በተዘጋጀው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ በቂ ገንዘብ የተገኘ መሆኑም ከስፍራው ከተገኘው ማስረጃ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በገቢ ማባሰቢያው ላይ አቶ አሰፋ ኃብተወልድ የመኢአድን አገር አቀፋዊ እንቅስቃሴን አስመልክተው ንግግር ያደረጉ ሲሆን አደረጃጀትና ድርጅታዊ ጉዳይን በሚመለከት ደግሞ መቶ አለቃ ወንድም ለተሳታፊዎች ገለጻ አድርገዋል፡፡
የምስራቅ ጐጃም ዞን አደራጅ አቶ ተስፋዬ ታሪኩ፣ የምስራቅ ጐጃም ዞን ስራ አስፈጻሚና ሰብሳቢ መቶ አለቃ ዮሐንስ አባተ፣ የደጀን ወረዳ የሴቶችና የወጣቶች ጉዳይ ሐላፊዎች የመኢአድ የወረዳ ድርጅታዊ አሰራርን በተመለከተ ሰፊ ገለጻ አቅርበዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከሰባት ወረዳዎች የመጡ የወረዳ ሰብሳቢዎችም የየወረዳቸውን እንቅስቃሴ በተመለከተ ሪፓርታቸውን አሰምተዋል፡፡
በዝግጅቱ ፍጻሜ ላይ የእስልምናና የክርስትና ሐይማኖት አባቶች በየተራ የመዝጊያ ንግግርና ሐይማኖታዊ ምርቃት ሰጥተዋል፡፡ መኢአድም እንዲጠናከር ሠፊ ምክር ለግሰው ስብሰባው ተጠናቋል፡፡