የመኢአድ የአርባ ምንጭ ዞን ሰብሳቢና ፀሐፊ ያለ ሕግ አግባብ ታሰሩ
በጋሞ ጐፋ የአርባ ምንጭ ዞን የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ ሰብሳቢ አቶ ገዛኸኝ ገለቱ እና ፀሐፊው አቶ ሙሉጌታ ወንድሙ መጋቢት 1 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በአርባ ምንጭ ከተማ በሲቀላ ክፍለ ከተማ ፓሊስ ጣቢያ የታሰሩ መሆናቸውን ተገለፀ፡፡
የዞኑ የመኢአድ ሰብሳቢና ፀሐፊ በገዥው ፓርቲ ባለሥልጣናት ለመታስር ያበቃቸው ምክንያት ምልክት ያለበትን ሰንደቅ ዓላማ አልሰቀላችሁም በሚል ሰበብ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የገዥው ፓርቲ ሰዎች ሶስት ቀለማት ብቻ ያለበትን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አውርደው የት እንዳደረሱትም ያልታወቀ መሆኑን ከቦታው የደሰረሰን መረጃ ያስረዳል፡፡
ከዚህ በፊትም በጐፋ ልዩ ዞን ጐፋ ወረዳ መኢአድ ጽ/ቤት ይውለበለብ የነበረውን አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ቀለማት ያሉትን ነባር የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ምልክት የለበትም በማለት የወረዳው ፖሊሶች አውርደው መውሰዳቸው ይታወቃል፡፡
መኢአድ በመካኩሉ ኮኮብ የሌለበትን የኢትዮጵያ ባንዲራ ላለፉት አምስት አመታት ሲጠቀምበት የሚታወቅ ሲሆን የካቲት 20 2001 ዓ.ም. በተላለፈው የአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ በዞኑ በመኢአድ ላይ በመንግሥት የጸጥታ አባላት የሚፈጽሙትን ሕገ ወጥ ጫና አስመልክቶ አቶ ገዛኸኝ ገለቱ ቃለ መጠይቅ መስጠታቸው ለመታሠራቸው እውነተኛው ምክንያት እንደሆነ አስተያየት ሰጭዎች ይገልጻሉ።
ግለሰቦቹ የታሰሩት ያለ ፍርድ ቤት ማዝዣ ሲሆን በታሠሩ በሦሥተኛው ቀን በዋስ መለቀቃቸውን ከቦታው የደረሰን መረጃ ይጠቁማል።